በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አሉ የሚባሉ ቅራኔዎች
‹ወደ ፍርድም አስቀድሞ የገባ ፃድቅ ይመስላል፣ ባላጋራው መጥቶ እስኪመረምረው ድረስ› ምሳሌ 18.17

የቅራኔዎች መኖር ውንጀላ
በ Jay Smith, Alex Chowdhry, Toby Jepson, James Schaeffer

[ክፍል አንድ] [ክፍል ሁለት] ክፍል ሦስት [ክፍል አራት]

ትርጉምና ቅንብር በአዘጋጁ

ስድስተኛ፡ ኢዮአኪን መንገስ በጀመረ ጊዜ የስምንት ዓመት ወይንስ አስራ ስምንት ዓመት ጎልማሳ ነበር?

በ2 ነገስት ምዕራፍ 24.8 ላይ “ዮአኪን መንገሥ በጀመረ ጊዜ የአሥራ ስምንት ዓመት ጕልማሳ ነበረ፤” በ2ዜና 36.9 ላይ ደግሞ “ዮአኪንም መንገሥ በጀመረ ጊዜ የአሥራ ስምንት ዓመት ጕልማሳ ነበረ፥” (የ2 ዜና 36.9 በእንግዚአኛው “የስምንት ዓመት ጎልማሳ ይላል) የሚለውን እናገኛለን፡፡ ዩአኪን በኢየሩሳሌም ላይ መንገስ ሲጀምር የ18 ዓመት ነበር ወይንስ የ8 ዓመት?  የዚህ ዓይነቱ ስህተት የጸሐፍቱ የቅጂ ስህተት ውስጥ ሊመደብ የሚችል ነው፡፡

አሁንም እንደገና ስለ ሁለቱ አንቀፆች እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ማስረጃዎች በአውዶቻቸው ውስጥ ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ስምንት ዓመት የሚለው ስህተት ሲሆን 18 ዓመት የሚለው ግን ትክክል ነው፡፡ (የ1962 የአማርኛ ትርጉም በሁለቱም ቦታዎች ላይ አስራ ስምንትን አስቀምጧል) ዩአኪን መንገስ በጀመረ ጊዜ ስምንት ዓመቱ ነበር የሚለው የመንግስትን ስልጣን ሃላፊነት ለመውሰድ ብዙውን ጊዜ ለመገመት አስቸጋሪ የሆነ በጣም የወጣት ዕድሜ ነው፡፡ ይሁን አንጂ አንዳንድ ተንታኞች ይህም ሙሉ ለሙሉ ይቻል እንደነበረ ይናገራሉ፡፡ እነርሱም የሚይዙት አቋም ዩአኪን የስምንት ዓመት ልጅ በነበረበት ጊዜ አባቱ እርሱን አብሮ ገዢ አደረገው የዚህ ምክንያቱም መንግስት የመምራት ሃላፊነትን እንዲማርና እንዲለማመድ ነበር ይላሉ፡፡ ዩአኪን ከዚያም በኋላ በግልጥ ንጉስ ሆኖ የነበረው በአስራ ስምንት ዓመቱ ነው ይላሉ ያም አባቱ እንደሞተ ማለት ነው፡፡

ይሁን እንጂ በጣም አሳማኝ የሚመስለው እይታ የሚሆነው በቁጥሮች ዙሪያ ላይ ያተኮረ ሌላ የጸሐፍት ወይንም የቀጅዎች ስህተት ምሳሌ እንደሆነ ነው፡፡ በዕብራይስጥ ቋንቋ አጻጻፍ ውስጥ ሦስት ዓይነት የቁጥር አጻጻፎች እንደነበሩ  እዚህ ላይ መጠቆም በጣም ጠቃሚ ይሆናል፡፡ ጥንታዊው እና ተከታታይ የሆኑት ዘገባዎች በአይሁድ ሰፋሪዎች በ5ኛው መቶ ዓ.ዓ. እና የኤሌፋንታይን ፓፔሪ የሚባሉት (ከዚህ በታች በጣም በዝርዝር ገልጠውታል) ለቁጥሮች የፊደላትን የመጠቀም ስነ ዘዴን ይከተሉ ነበር፡፡ ተጨማሪ ስነ ዘዴዎች ከቁጥሮቹ ውስጥ ያሉት ፊደላትን በሙሉ የመጠቀምም ተጨማሪ ስነዘዴ በጸሐፍቱ ማህበር ውስጥ እንዲገባ (እንዲጀመርም) ተደርጎ ነበር፡፡ ሆኖም በፓፒረስ የተመዘገቡ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ማስረጃዎች ውስጥ ልንጠቅስ የምንቻላቸው ሦስት የማስረጃ ምንጮች አሉን፡፡

እንደ እነዚህ ዓይነት ብዙ የቁጥር ልዩነቶችን በተመለከተ ልዩነትን ያሳየው “በአስራ ቤቶች” ውስጥ የሚገኙት ቁጥሮች ናቸው፡፡ ለዚህም በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ውስጥ ከጌታ ልደት በፊት የአይሁድ ሰፋሪዎች ይጠቀሙባቸው የነበሩትንና በኤሌፋንታይን ፓፔሪ ላይ የሚገኙትን የቁጥሮችን አጠቃቀም መመልከት ትምህርት ሰጪ ነው፡፡ በእዝራ እና በነህምያ ዘመን፤ ማለትም ይህ ክፍል ከመጣበት ጊዜ ያለው ሁኔታ የጥንቱን የቁጥር አጠቃቀምን ምስክርነት ይሰጣል፡፡ ይህ ደግሞ የያዘው ቁጥሮችን በአስራዎች ቤት ውስጥ ለማስቀመጥ አግድማዊ መስመር በስተቀኝ ወደ ታች የሚወርድ ማለትም እንደ ፊደል “ገ” ዓይነት ጽሑፍ የአስራቤቶችን ለመወከል ያስቀምጣቸዋል (ስለዚህም ሁለት አግድም መስመሮች አንዱ በሌላው ላይ 20 ይሆናል ማለት ነው)፡፡ ቀጥ ያሉ መስመሮች ደግሞ ማንኛውንም ከአስር በታች ያለውን ቁጥር ይወክሉ ነበር፡፡ ስለዚህም ስምንት ሊሆን የሚችለው (/III IIII) ነገር ግን አስራ ስምንት ይሆን የነበረው በእነዚህ በላይ በተሰመረ አግዳሚ መስመርና በስተቀኝ በኩል በወረደ ሌላ መስመር ነበር፡፡ በተመሳሳይም መንገድ ሃያ ሁለት ይሆን የነበረው /I ይህ ከተጨማሪ አግድማዊ መስመርና በስተቀኝ በኩል በወረደ ተንጠልጣይ መስመር ይሆንና በተመሳሳይም መንገድ አርባሁለት የሚሆነው /I እና ሁለት አግድማዊ መስመሮች ከግራ በኩል ወራጆቻቸው ጋር ነበር ማለት ነው (ገለፃው ሙሉ ለሙሉ የሚፈለገውን ባያሳይም ጉዳዩ አገልግሎት ላይ የዋለው በዚህ መልኩ ነበር)፡፡

እንዲህ ከሆነ ደግሞ የመጀመሪያው ጽሑፍ ኮፒ ይደረግበት የነበረው ደብዛዛ ወይንም ያልጠራ ቢሆን ኖሮ የአስርቶች ማሳያ ሊሆኑ የሚችሉት አንዱ ወይንም ብዙዎች በቅጂዎቹ ጸሐፍቱ ሊዘለሉ ይችሉ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ጸሐፊው ተጨማሪ መስመሮችን ከመጨመሩ ይልቅ የነበሩትን ማጥፋቱና አጠቃላይ ቅነሳውን ማድረጉ ይቀለው ነበረ ማለት ነው፡፡

የዚህ የቁጥር ልዩነት መኖር ጉዳይ የመጽሐፍ ቅዱስን የእግዚአብሔር ቃልነት በምንም መልኩ የሚያቃልልና የሚያጣጥል ሊሆን አይችልም፡፡ ከዚህም በላይ አንድም የትርጉም ወይንም የመሰረታዊ ትምህርት ችግር አያመጣም፡ አላመጣምም፤ ለእውነተኛ ክርስትያኖች ያስከተለውም ጥርጥር በጭራሽ አልታየም፡፡ የዚህ ዓይነት የኮፒ አድራጊዎች ስህተት በሌሎች እምነት ጽሑፎች በታሪክም መጽሐፍት ውስጥ ሁሉ የሚገኝ ነው፡፡

ለምሳሌም ያህል በሂፁን የድንጋይ ጽሑፍ ላይ በቀዳማዊ ዳርዮስ የተቀመጠው ላይ የምናነበው ነገር በተራ ቁጥር 38 ላይ በፍራዳ ጦር ሰራዊት የታገደሉት ወታደሮች 55,243 ሲሆኑ 6,572 ደግሞ ተማርከው ነበር ይህም በባቢሎናውያን ስር ነበር፡፡ የዚህ ጽሑፍ ኮፒ በባቢሎን በራሱ የተገኘው የታሰሩት ምርኮኞች ቁጥር 6,973 ነው ይላል፡፡ ይሁን እንጂ በአርማይኩ ትርጉም ላይ በኤልፋንታይን በግብፅ የተገኘው ማስረጃ የሚናገረው የታሰሩት ምርኮኞች ቁጥር 6,972 ነው ይላል፡፡

በተመሳሳይም በቁጥር 31 ባለው ተመሳሳይ ጽሑፍ ላይ የባቢሎናውያኑ ዘርፍ የሚሰጠው ማስረጃ 2,045 እንደተገደሉት ወታደሮች ሲሆን፤ በፍራዋቲሰሀ ጦር ሰራዊት ያመፁት የተገደሉት ሲሆን፤ የተማረኩት እስረኞች ቁጥር ደግሞ 1,558 ናቸው ሲል የአርማይኩ ደግ ከ1,575 በላይ የተማረኩ እስረኞች መኖራቸውን ዘግቧል፡፡

(ከዚህ በላይ ላለው ምሳሌያዊ ታሪካዊ ማስረጃ ሎጂካል መልስ መስጠት ከባድ ሲሆን የመጽሐፍ ቅዱሱ ላይ ላለው ግን ሎጂካል መልስ ለመስጠት ግን በምንም ዓይነት መንገዱ አስቸጋሪ አይሆንም የትምህርትና የትርጉም ችግርም አያስከትልም፡፡)

ሰባተኛ፡ ዩአኪን የነገሰው ለሦስት ወር ወይንስ ለሦስት ወር ከአስር ቀናት ነበር?

በ2 ነገስት 24.8 ላይ ዮአኪን “በኢየሩሳሌምም ሦስት ወር ነገሠ” ሲል በ2ዜና 36.9 ደግሞ፤ ዮአኪንም “በኢየሩሳሌምም ሦስት ወርና አሥር ቀን ነገሠ” የሚልን ልዩነት እናገኛለን፡፡ ስለዚህም ጥያቄው ኢዮአኪን የነገሰው ሦስት ወር ነው ወይንስ ሦስት ወር ከእስር ቀን ነው?

እዚህ ላይ እንደገና ከዚህ በላይ በተራ ቁጥር 2 እና 4 ላይ እንዳየነው፣ የዜና መዋዕል ጸሐፊ በአቆጣጠሩ (በቁጥር አሰጣጡ) በጣም ዝርዝር ድረስ ሲሄድ የነገስት ጸሐፊ ግን የጊዜውን ቁጥር ከወራቶቹ ቁጥር ጋር አጠጋግቶ ብቻ ነው ያስቀመጠው፣ ይህም ተጨማሪዎቹ አስር ቀናት ለመጠቀስ ያን ያህል ጠቃሚ አለመሆናቸውን በማሰብ ነው፡፡

ስምንተኛ፡ ኃያሉ ሰው የገደለው ሦስት መቶ ሰው ወይንስ ስምንት መቶ ሰው?

በ2 ሳሙኤል 23.8 ላይ “የዳዊት ኃያላን ስም ይህ ነው። የአለቆች አለቃ የሆነ ከነዓናዊው ኢያቡስቴ ነበረ፤ እርሱም ጦሩን አንሥቶ ስምንት መቶ ያህል በአንድ ጊዜ ገደለ።’ በ1 ዜና 11.11 ላይ ደግሞ “የዳዊትም ኃያላን ቍጥር ይህ ነበረ፤ የሠላሳው አለቃ የአክሞናዊው ልጅ ያሾብአም ነበረ፤ እርሱ ጦሩን አንሥቶ ሦስት መቶ ሰው በአንድ ጊዜ ገደለ።’ የሚለውን ጽሑፍ እናነባለን፡፡

ጥያቄው ስሙ የተጠቀሰው ኃያል ሰው ስንት ሰዎችን ነው በአንድ ጊዜ የገደለው የሚለው ነው፡፡ ለዚህ መልሱ በዚህ ቦታ ላይ ሁለቱም ጸሐፊዎች የተለያዩ ክስተቶችን እየገለፁ ሊሆን የሚችል ነገር ነው፡፡ ይህም ምንም እንኳን ነገሩ የተደረገው በአንድ ሰው ቢሆንም ጭምር ነው፡፡ ወይንም ደግሞ አንድ ጸሐፊ በአንድ ሰው የተደረገውንም ነገር በከፊልም ሲያቀርብ ሌላው በሙሉም አቅርቦት ሊሆን እንኳን ይችላል፡፡

የሆነው ሆኖ ይህ አይነቱ በቁጥር መዛባት ላይ ያለው ችግር የታሪክን አውድ ወይንም የጸሐፊውን ዓላማ ካለመረዳት የሚመጣ ችግር ነው፡፡ (ከዚህም በፊት እንደተጠቆመው ሁሉ እንዲህ ዓይነት ችግሮች  አጠቃላይ የትምህርት መዛባት ወይንም መሰረታዊ ትምህርት ላይ ወይንም ደግሞ ትርጉም ላይ የሚያመጡት ችግር የለም፡፡)

ዘጠነኛ፡ የቃል ኪዳኑ ታቦት ወደ ኢየሩሳሌም የተወሰደው መቼ ነበር?

በ2 ሳሙኤል 5 እና 6 መሰረት ዳዊት የቃል ኪዳኑን ታቦት ወደ ኢየሩሳሌም የወሰደው ፍልስጥኤማውያንን ድል ካደረገ በኋላ ነው ወይንስ በ1ዜና ምዕራፍ 13 እና 14 መሰረት ከጦርነቱ በፊት ነበር?

እንዲህ ዓይነቱ ቅራኔ እንዳለ ተደርጎ የሚቀርበው አጠቃላይ ክፍሉን ካለማንበብና አውዱንም ካለመረዳት የተነሳ ነው፡፡

ይህም ለክስትያኖች በእውነት ችግር አይደለም፡፡ ይህንን እንደ ችግር ያነሳው ሻቢር አላይ 1ዜና ምዕራፍ 15 ድረስ ቀጥሎ ማንበብ ነበረበት፣ እንዲያ ቢያደርግ ኖሮ ዳዊት የቃል ኪዳኑን ታቦት ፍልስጥኤማውያንን ካሸነፈ በኋላ ሲያመጣ ይመለከተው ነበር፡፡ ለዚህም ምክንያቱ እስራኤላውያን የቃል ኪዳኑን ታቦት ሁለት ጊዜ ማንቀሳቀሳቸው ነበር፡፡ በመጀመሪያም ፍልስጥኤማውያንን ከማሸነፋቸው በፊት ከበዓል ስፍራ አንቀሳቅሰውት ነበር በ2ሳሙኤል 5 እና 6 ላይ እንደምናየው እንዲሁም በ1ዜና 15 ላይ፡፡ አንድ ጊዜ ነቢዩ ሳሙኤል ዳዊት በፍልስጥኤማውያን ላይ ያገኘውን ድል ከዘገበ በኋላ የቃል ኪዳኑ ታቦት ሁለት ጊዜ እንደተንቀሳቀሰ ደግሞ ይነግረናል፡፡ ይሁን እንጂ በ1ዜና ላይ ያለው ቅደም ተከተል እንደሚከተለው ነው፡ የቃል ኪዳኑ ታቦት በቅድሚያ ወደ በዓል ተንቀሳቀሰ፣ ከዚያም ዳዊት ፍልስጥኤማውያንን ድል አደረገ እናም በመጨረሻ ላይ የቃል ኪዳኑ ታቦት ከዖቤድ-ዶም ቤት ተንቀሳቀሰ፡፡

ስለዚህም ሁለቱ ዘገባዎች እርስ በእርሳቸው በፍፁም የሚቃረኑ አይደሉም፡፡ እዚህ ላይ ያለን ነገር በቀላሉ ነቢዩ የቃል ኪዳኑን ታቦት በተመለከተ በአንድ ጊዜ አጠቃላዩን ታሪክ ሲሰጠን ነው (ይህም በኋላ ስለ እርሱ ከመጥቀስ ይልቅ ነው) እንዲሁም ሌላው ደግሞ ታሪኩን በተለየ መንገድ ሲያቀርበው ነው፡፡ በሁለቱም መንገድ የክስተቶቹ ጊዜዎች ተመሳሳይ ናቸው፡፡

ይህንን በተመለከተ ስለ ቁርአንም ተመሳሳይ ቅራኔ ነገር አለ ሊባል ይቻላል፡፡ (እዚህ ነጥብ ላይ ሁሉንም መጥቀስ ባይቻልም) በቁርአን ምዕራፍ 2 ላይ እኛ የተነገረን ነገር ስለ አዳም ውድቀት ነው፣ ከዚያ እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ምህረት ሲያደርግ ይታያል፤ ይህም የፈርዖንን በባህር መስጠም ተከትሎ ነው፣ እንዲሁም የሙሴ ነገር ሲቀጥልና የወርቁ ጥጃ ታሪክ፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ደግሞ እስራኤላውያን ስለ ምግበብና ስለ ውሃ ሲያጉረምርሙ ይታያሉ፤ ከዚያ በኋላ ስለ ወርቁ ጥጃ ዘገባ እንደገና እናገኛለን፡፡ ከዚህም ቀጥሎ ስለ ሙሴና ስለ ኢየሱስ እናነባለን ከዚያም ስለ ሙሴና ስለወርቁ ጥጃ እንደገና እናነባለን፣ ከዚያም ደግሞ ስለ ሰሎሞንና ስለ አብርሃም፡፡

አንድ ሰው ስለ ቅደም ተከተል መናገር ከፈለገ ሙሴ ከኢየሱስ ጋር ምን የሚያገናኘው ነገር አለ ወይንም ሰሎሞን ከአብርሃም ጋር ምን ያገናኘዋል? ቅድም ተከተልን በተመለከተ የቁርአኑ ምዕራፍ ሁለት ማቅረብ የነበረበት ነገር ቢኖር ከአዳም ውድቀት በኋላ፤ የቃየንን፤ ከዚያም የአቤልን፤ የሄኖክን፤ የአብርሃምን፤ የሎጥን፤ የይስሐቅን፤ ቀጥሎም የያቆብንና የኤሳውን ከዚያም የዬሴፍን ቀጥሎም የእስራኤል ልጆችንና ሙሴን በዚያ ቅደም ተከተል ማቅረብ ነበረበት፡፡ እንዲህ ዓይነት ዝብርቅርቁ የወጣ የቅደም ተከተል ድብልቅ በዚያ አንድ የቁርአን ምዕራፍ ከተገኘ፤ ሻቢር አላይ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስህተት ወይንም ቅራኔ የሚመስሉ ነገሮችን እያነሳ ለማስረዳት ከመነሳት በፊት፤ በቁርአኑ ውስጥ ያሉትን እነዚህን ድብልቅልቆች ለማስረዳትና ሰዎች እንዲቀበሏቸው ለማድረግ ጥሩ ስራ መስራት ነበረበት ፡፡

አስረኛ፡ ወደ መርከቡ ውስጥ የገቡት እንሰሶች ሁለት ጥንድ ወይንስ ሰባት ጥንድ?

ኖህ ከእያንዳንዱ ሕይወት ያለው እንሰሳ ሁለት፤ ሁለት ነበርን ያመጣ የነበረው በዘፍጥረት 6.19-20 ላይ ወይንስ በዘፍጥረት 7.2 መሰረት ንፁህ ከተባሉት እንሰሶች ሰባት ወንድና ሴት እንስሰሶችን ነበር? እንዲሁም ይህን በተመለከተ ዘፍጥረት 7.8 እና 9 ተመልከቱ፡፡

(እንዲህ ዓይነቱ ቅራኔ ክፍሉን በተሳሳተ መንገድ ከመጥቀስ የመጣ ችግር ነው፡፡)

ይህ በእርግጥ ለማንሳት በጣም ጥሩ ያልሆነ ጥያቄ ነው፡፡ ሻቢር አላይ በዘፍጥረት 6 ላይ ያለውን ክፍል አሳስቶ መጥቀሱ በጣም ግልፅ ነው፣ በዚያም ላይ ንፁህ የተባሉት እንስሳት በምንም መንገድ አልተጠቀሱም ነገር ግን በሰባተኛው ምዕራፍ ላይ በንፁህና ንፁህ ባልሆኑት እንሰሳዎች መካከል በተለየ ሁኔታ ልዩነት ተደርጓል፡፡ ዘፍጥረት 7.2፤3፤ “ከንጹሕ እንስሳ ሁሉ ሰባት ሰባት ተባትና እንስት፥ ንጹሕ ካልሆነ እንስሳም ሁለት ሁለት ተባትና እንስት፥ ከሰማይ ወፍ ደግሞ ሰባት ሰባት ተባትና እንስት እያደረግህ በምድር ላይ ለዘር ይቀር ዘንድ ለአንተ ትወስዳለህ።” ይላል፡፡ ሻቢር ታዲያ ሁለት ጥንድ በሚለውና በሰባት ጥንድ መካከል ቅራኔ አለ ለማለት ሲነሳና ጥያቄውን ሲያቀርብ ስለ ምንድነው የክፍሉን ሁለተኛ ክፍል ማለትም ንፁህ ካልሆኑት ሁለት ጥንድ የሚለውን ያልጠቀሰው? በሁለቱ ዘገባዎች መካከል ምንም ቅራኔ የሌለ መሆኑ በጣም ግልጥ ነገር አይደለምን? ችግሩ ያለው በጥያቄው በራሱ ላይ ነው፡፡

ሻቢር የራሱን ነጥብ ለማስረዳት የምዕራፍ ሰባትን ሁለት ቁጥሮች ማለትም ቁጥር 8 እና 9 ጠቅሶ ወደ መርከቡ ውስጥ የገቡት ሁለት ጥንዶች ብቻ ናቸው ይላል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ ጥቅሶች ሁለት ጥንድ ብቻ ወደ መርከቡ ገቡ በማለት የሚናገሩት ምንም ነገር የላቸውም፡፡ እነሱ በግልጥ የሚናገሩት ነገር ቢኖር ወደ መርከቡ ውስጥ የገቡት የንፁህ እንሰሶች ጥንዶችና ንፁህ ያልሆኑት እንሰሶች ጥንዶች ናቸው በማለት ብቻ ነው፡፡

ከንፁሆቹ እንሰሳት ሰባት ጥንድ የተፈቀደበት ምክንያት በትክክል ግልፅ ነው፤ እነርሱ ውሃው ከጎደለ በኋላ ለአምልኮው መስዋዕት እንዲቀርቡ አገልግሎት ላይ የሚውሉ ነበሩ (በእርግጥም በዘፍጥረት 8.20 ላይ በዚያ አገልግሎት ላይ ውለዋል)፡፡ በግልፅ እነዚህ ንፁህ እንሰሳት ከሁለት ጥንድ በላይ ባይኖሩ ኖሮ፣ እነርሱ በመሰዊያው ላይ በመሰዋታቸው ከምድር ላይ ጠፍተው ነበር ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ንፁህ ባልሆኑት እንሰሳት ወፎች አንድ ጥንድ ብቻ በቂ ይሆን ነበር ምክንያቱም እነርሱ ለደም መስዋዕት አይፈለጉም ነበርና፡፡

አስራ አንደኛ፡ የፈረሰኞቹ ቁጥር ስንት ነበር?

በ2 ሳሙኤል 8.4 መሰረት ‘ዳዊትም ከእርሱ ሺህ ሰባት መቶ ፈረሰኞች፥ ሀያ ሺህም እግረኞች ያዘ፤’ በማለት ሲናገር በ1 ዜና 18.4 ላይ ግን “ዳዊትም ከእርሱ አንድ ሺህ ሰረገሎች፥ ሰባት ሺህም ፈረሰኞች፥” የሚለውን እናገኛለን የትኛው ነው ትክክል?

(ይህ ችግር በጸሐፍት ስህተት ውስጥ የሚካተት ዓይነት ነው፡፡)

እነዚህ የ1,700 እና የ7,000 ፈረሰኞች የቁጥር ልዩነቶችን በተመለከተ ሁለት የሚቻሉ መልሶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ የመጀመሪያው ኬል እና ደሊዚሽ በ(ገፅ 360) ላይ የሰጡት በጣም አሳማኝ መፍትሄ ነው፡፡ እነርሱም የያዙት አቋም ለሰረገላ ጥቅም ላይ ውሎ የነበረው ቃል (ረከብ) በ2 ሳሙኤል 8.4 ላይ በጸሐፍቱ ሳይታወቅ (ሆነ ሳይባል) እንደተዘለለ ነው፡፡ እንዲሁም ሁለተኛው ቁጥር 7,000 (ለፈረሰኞቹ) እንዲሁም እርሱ ጸሐፊው ያየው በቀላሉ 1,000 ከጻፈ በኋላ ማንም ሰው 7,000 አይጽፍም በማለት ነው ይህም አንድና ተመሳሳይን ቁጥር ካስቀመጠ በኋላ ነው፡፡ የሰረገላዎቹ መዘለል በቀደሙት ጸሐፍት የተደረገ ሳይሆን አይቀርም እንዲሁም ከ7,000 ወደ 700 የተደረገው ቅነሳ ከዚያ በኋላ በተከታታይ በመጡ ጸሐፍት እንዳለ እንዲቀጥል ሳይደረግ አልቀረም፡፡ ነገር ግን በሁሉም ዓይነት መንገድ ሲታይ የ1 ዜና ቁጥር ትክክል ነው እናም የ1ሳሙኤል ቁጥር ከዜና ቁጥር ጋር እንዲስማማ ከዚያ አንፃር መስተካከል ይኖርበታል፡፡

ሁለተኛው መልስ (መፍትሄ) የሚጀምርበት ሐሳብ ቁጥሩ ወደ 700 የተቀነሰው 700 መደዳዎችን ስለሚጠቅስ ነው የሚል ነው እያንዳንዱም መደዳ የያዘው 10 ፈረሰኞችን ስለ ሆነ በአጠቃላይ 7000 ይሰጣል የሚል ነው፡፡

አስራ ሁለተኛ፡ አራት ሺ ወይንስ አርባ ሺ ጋጦች?

በ1ነገስት 4.26 ላይ “ለሰሎሞንም በአርባ ሺህ ጋጥ የሚገቡ የሰረገላ ፈረሶች አሥራ ሁለት ሺም ፈረሰኞች ነበሩት።’ በ2ዜና 9.25 ላይ ደግሞ ሰሎሞንም “ለፈረሶችና ለሰረገሎች አራት ሺህ ጋጥ፥ አሥራ ሁለት ሺም ፈረሰኞች ነበሩት፥” ይላል፣ እዚህ ላይ የሚነሳው ጥያቄ አርባ ሺ ወይንስ አራት ሺ ጋጦች ነበሩ የሚለው ነው፡፡

(ይህ ችግር የጸሐፍቱ ስህተት ወይንም ደግሞ የታሪካዊ አውድ አለመገንዘብ የመጣ ነው፡፡)

ይህንን ልዩነት ለመረዳት የተለያዩ ሎጂካል መንገዶችና መልሶች ይገኛሉ፡፡ በጣም አሳማኙ ግን ከዚህ በፊት በቅራኔ አምስትና ስድስት ካየናቸው ነጥቦች ጋር አብሮ የሚሄድ ነው፡፡ ይህም የእስራዎቹ ቤቶች ቁጥሮች ተፈግፍገው ጠፍተዋል ወይንም በተደጋጋሚ ጥቅም ላይ መዋል የተነሳ ጠፍተዋል የሚለው ነው፡፡

ሌሎች የሚጠቅሱት በ2 ዜና ላይ የተጠቀሱት ጋጦች ትልልቆችና እያንዳንዳቸው 10 ፈረሶችን የሚይዙ ነበሩ (ማለትም አስር አስር የጋጦች መደዳዎች) ስለዚህም 4,000 የሚሆኑት እነዚህ ትልልቅ ጋጦች 40,000 የሚሆኑ ትናንሽ ጋጦች ጋር እኩል የሚሆኑ ናቸው የሚል ሎጂካዊ ገለጣ ነው፡፡

ሌላ ተንታኝ እንዳለው በ1 ነገስት ላይ የተጠቀሰው የጋጦች ቁጥር ንጉሱ ሰለሞን መንገስ ሲጀምር የነበረ ሲሆን በ2 ዜና ላይ የተጠቀሰው ግን በንግስናው ጊዜ መጨረሻ ላይ ነው፡፡ እንደምናውቀውም ሰሎሞን የገዛው ለ 40 ዓመታት ያህል ነው ስለዚህም በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ያለምንም ጥርጥር እጅግ በጣም ብዙ ለውጦች ተከናውነዋል፡፡

የአዘጋጁ ማሳሰቢያ፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አሉ ከሚባሉት የእርስ በእርስ ቅራኔዎች ውስጥ ከዚህ በላይ ያየናቸው ከቁጥር ጋር የተያያዙ ብቻ ናቸው፡፡ ሕትመት በሌለበት፤ ጽሑፎችና መጽሐፎች ሁሉ በእጅ ጸሐፊዎች ይገለበጡ በነበሩባቸው ጊዜያት እንዲህ ዓይነት ጥቂት እጅግ በጣም ጥቂት ልዩነቶች መኖራቸው አስደናቂ አይሆንም፡፡

በጣም የሚያስደንቀው ግን የቁጥሮቹ ልዩነቶች መከሰታቸውን በተመለከተ የምንገነዘባቸው እውነታዎች ናቸው፡፡ እነርሱም ለእያንዳንዱ ልዩነቶች ሎጂካዊ የሆነ መልስን ማግኘት የሚቻል መሆኑ አንዱ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የቁጥሮቹ ልዩነቶች በመሰረታዊ ክርስትና እምነት ላይ የሚያመጡት ምንም ችግርና ተፅዕኖ በጭራሽ አለመኖሩ ነው፡፡

ይህም እውነታ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑንና በሰዎች ሊነሳ ከሚችልና በሰዎች ከሚከሰት ችግር ሁሉ በላይ በመለኮታዊ ጥበቃ መጠበቁንም ያሳየናል፡፡

ከዚህ የተነሳ ለአንባቢዎች የምናሳስበው ነገር፣ የቀረቡትን ማስረጃዎች በቅንነት እንዲመለከቱና፣ “መጽሐፍ ቅዱስ ቅራኔ አለው” በሚል የተሳሳተ ሐሳብ በተለያዩ ሰዎች የቀረቡት ውንጀላዎች ሁሉ ትክክል አለመሆናቸውን እንዲገነዘቡ ነው፡፡ በመሆኑም ለመንፈሳዊ ሕይወት መሰረት የሆነውን፣ የሰው ልጅ ሕይወት አሁን ያለበት ሁኔታ ምክንያቱ ምን እንደሆነ የሚገልፀውንና ለዚህም መፍትሔ የሚሰጠውን ቃል፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል እንድታነቡ እንጋብዛችኋለን፡፡

የሚከተሉት ጥያቄዎች መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብና መልስ ለመፈለግ ጠቃሚዎች ናቸው እነዚህም፡ በዘመናትና ሁሉ ውስጥና በአሁኑ ጊዜ ያለውን የሰው ልጅ መሰረታዊ ችግር መጽሐፍ ቅዱስ ምንድነው ይላል? ለዚያስ መሰረታዊ ችግር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው መፍትሔ ምንድነው? መጽሐፍ ቅዱሳዊውን መፍትሔ ሰዎች ሊያገኙና ሊጠቀሙበት የሚችሉት በምን ሁኔታ ውስጥ ነው?

ለእነዚህ መሰረታዊ ጥያቄዎች መልስን ማግኘት ትልቅ ዕድል ነው፣ የሰው ልጅ ሁሉ ሊያስብበት የሚገባም ጉዳይ ነው ስለዚህም ለእነዚህ መሰረታዊ የሕይወት ጥያቄዎች መልስን ለማግኘት መጽሐፍ ቅዱስን ፈልጋችሁ አግኙና አንብቡት፡፡ ጌታ እግዚአብሔርም በፀጋው ይርዳችሁ፣ በቃሉም ይናገራችሁ አሜን፡፡

የትርጉም ምንጭ: "101 Cleared-up Contradictions in the Bible"

ለእስልምና መልስ አማርኛ  ዋናው ገጽ